ኢዜአ/ሐረር/ 22/ 02/2009 የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በራስ ተነሳሽነት ብር በማዋጣት የገዟቸውን 3ሺ የማጣቀሻ መጽሐፍቶችን በአካባቢው ለሚገኙ ትምህርት ቤቶች ዛሬ ለገሱ።
መጽሃፍቶቹ በትምህርት ቤቶቹ ውስጥ የሚታየውን የማጣቀሻ መጽሃፍት እጥረቶችን በመቅረፍ ተማሪው የተሻለ ውጤት እንዲያመጣ ትልቅ እገዛ ያደርጋል ሲሉ መምህራንና ተማሪዎች ይገልጸሉ።
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ከመማር ማስተማርና ከምርምር ስራዎች ባለፈ ባለፈ የአካባቢውን ማህበረሰብና ተቋም የማገልገል ትልቅ ሃላፊነት አለባቸው፤ የሐረማያ ከሚያከናውነው ስራ ጎን ለጎን ለበርካታ ዓመታት የአካባቢውን ነዋሪዎችና የመንግስት ተቋማትን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የማህበረሰብ አገልግሎት ላይ ዘርፈ ብዙ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል።

ይህንንም ለማጠናከር ተቋሙ ከሚያከናውነው ስራ በተጨማሪ ተማሪዎቹ በዋናው ግቢ በሚገኘው የማህበረሰበ አገልግሎት ክበብ አማካይነት ያዋጡትን 25 ሺህ ብር የማጣቀሻ መጽሃፍት በአካባቢው ለሶስት የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መለገሳቸውን የዩኒቨርሲቲው የተማሪዎች ህብረት ፕሬዝዳንት ተማሪ እንዳልካቸው አበራ ገልጿል።
ለዚህ ስራ መነሳሳት የፈጠረብን ዩኒቨርሲቲው ለማህበረሰቡ የሚያደርገው ስራና እኛም ተማሪዎች በአካባቢው ላይ ተምረን ዝም ብለን ከምንሄድ አንድ ነገር ሰርተን ለምን አናልፍም በማለት ይህን ስራ አከናውነናል።
በቀጣይም በአካባቢው የሚገኙ የመሰናዶና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ የቤተ ሙከራና የቤተ መጽሃፍት ክፍሎትን በዘመናዊ መንገድ ለመገንባት የተቋሙን የምህንድስና ተማሪዎች ክበብ ዲዛይን እንዲያወጡና የተለያዩ ክበባትንና ዩኒቨርሲቲው ደግሞ በጀት አፈላልገው ስራው እንዲጀመር እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን ተናግሯል።

በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ ልማት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር የማህበረሰብ ልማት ስራ ባለሞያ አቶ መኮንን ዳኜ  የዩኒቨርሲቲው የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት፣የተማሪዎች ህብረትና የተለያዩ ክበባት በቅንጅት የተለያዩ የማህበረሰብ አገልግሎት የድጋፍ ስራዎችን እያከናወኑ ይገኛሉ።

በአካባቢው ለሚገኙ የሐረማያ መሰናዶ፣ለባቲ ሁለተኛና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተሰጡት አጋዠ መጽሐፍቶችም የዚሁ አካል መሆናቸውን ጠቁመው፣ መጽሐፍቶቹም ተማሪው በዋናነት ከሚጠቀምበት በተጓዳኝ አጋዠ የሆኑና ጥሩ ድጋፍ የሚያደርጉ ናቸው።

ዩኒቨርሲቲው የሚያከናውነውን የድጋፍ ስራም በቀጣይ በገጠር ትምህርት ቤቶች ላይ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልና በተለይ ደግሞ ባለፉት ዓመታት ለመምህራንና ለተማሪዎች በየእሩብ ዓመቱ የሚሰጠው የአቅም ግንባታ ስልጠና እንዲሁም ቤተ መጽሐፍቶችንና ቤተ ሙከራዎችን የማስፋፋት ስራ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።

የሐረማያ መሰናዶ ትምህርት ቤት የፊዚክስ መምህር መስፍን ኤልያስ በመማር ማስተማር ስራ ላይ ከሚታየ ክፍተቶች መካለከል የአጋዠ መጽሃፍ እጥረት አንዱ ነው፤ በዛሬው እለት የተለገሱት መጽሃፍቶች ለተማሪውም ሆነ ለመምህሩ ያለው ጠቀሜታው የጎላ ነው።

መጽሃፍቶቹም ከጊዜው ቴክኖሎጂ ጋር የሚሄዱ፣በትምህርት ቤቱ የሚታየውን የአጋዠ መጽሃፍት ክፍተት የሚሸፍኑና መምህራኑና ተማሪው እንዲያነቧቸው የሚያነሳሱ ለመማር ማስተማር ስራ ምቹ ናቸው።

በትምህርት ቤቱ የሚገኙት የቤተ መጽሃፍትና ቤተ ሙከራ ክፍሎች ለማንበብያም ሆነ ተግባራዊ ትምህርት ለመስጠት ምቹ ስላልሆኑ በዚህ ላይ ዩኒቨርስቲው ድጋፍ እንዲያደግላቸው ጠይቀዋል።
የሐረማያ መሰናዶ ትምህርት ቤት የ12ኛ ክፍል ተማሪ ተመስገን ተሰማ መጽሃፍቶቹ በጣም ጥሩና ተማሪው የተሻለ ውጤት እንዲያመጣ አጋዠ ሆኖ የሚያገለግሉና ለትምህርት ቤታቸው በመሰጠቱ ደግሞ ደስታ እንደተሰማው ገልጿል።