ድሬደዋ መጋቢት 4/2009 የአለም የሴቶች ቀን እና ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የተጀመረበትን ስድስተኛ ዓመትን ምክንያት በማድረግ በሁለቱም ፆታ ከ1ሺህ በላይ ተማሪዎች የተሣተፉበት የሩጫ ውድድር ትናንት በሀረማያ ዩኒቨርሲቲ ተካሄደ፡፡

“የሴቶች የቁጠባ ባህል ማደግ ለህዳሴያችን መሠረት ነው” በሚል መሪ ሀሳብ ሶስት ኪሎሜትር በሸፈነውና በታዳጊ ወንዶች ምድብ ውድድር ዳዊት ሙሉጌታ ፣ገላን አብዱረህማን፣ነዲ አብዱልማሊክ  አንድ እስከ ሶስተኛ በመውጣት አሸንፈዋል፡፡ በሴቶቹ ደግሞ ሄለን አየለ፣ቤቴል አለምእሸት፣መባ ነጋሲ ተከታትለው በመግባት ውድድሩን በበላይነት አጠናቀዋል፡፡በአዋቂ ወንዶች ምድብ ደግሞ ገመቹ አዳሙ ፣ ኬናዋቅ ሙሌና ኑሪዬ አመዴ እንዲሁም  በሴቶች አመለወርቅ ብዙአየሁ፣ ገላኔ ፉፋ እና ሳሲ አለኬ ተከታታለው በመግባት አሸንፈዋል፡፡ በውድድሩ አሸናፊ ለሆኑ ከ1500 እስከ 3500 ብር ዋጋ ያላቸው ቦንድ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡  ሽልማቱን የሰጡት የሀረማያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዘዳንት ፕሮፌሰር ጨመዳ ፊኒንሳ ሴቶች ለሀገሪቱ የህዳሴ ጉዞ እውን መሆን እያበረከቱ የሚገኙትን ተግባራት ይበልጥ እንዲጎለብት ህብረተሰቡ ድጋፍ እንዲያደርግላቸው ጥሪ አቅርበዋል፡፡

ዩኒቨርስቲው ሴቶችን ለማበረታታት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል፡፡ የሴቶችን ጥቃትና ትንኮሳኔ በመከላከል የሴቶችን ውጤታማነት ለማረጋገጥ የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ  መጣር እንዳለበት ያመለከቱት ደግሞ የዩኒቨርሲው የአስተዳደርና የተማሪዎች ጉዳይ ምክትል ፕሬዘዳንት ዶክተር በላይነህ ለገሰ ናቸው ፡፡ ውድድሩ የሴቶችን የቁጠባ ባህልና የእርስ በርስ ግንኙነት ለማዳበር እንዲሁም ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የስፖርት ውድድር ከወዲሁ ብቃት ያላቸውን ሯጮች ለመለየት ጭምር ያገዘ መሆኑን የዩኒቨርሲቲው የህዝብና አለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ አለምእሸት ተሾመ ገልጸዋል፡፡