ኢዜአ/ሀረር  ሐምሌ 26/2006

መንግስት የታዳሽ ኃይል ኢነርጂን ለማስፋፋት የሚያካሂደውን ስራ ለማጎልበት በዘርፉ የሚካሄደው ጥናትና የምርምር ስራ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ።

በኃይል አቅርቦት፣ በአካባቢ ጥበቃና ዘላቂ ልማት ላይ ያተኮረ ሀገር አቀፍ ዓውደጥናት ከትናንት ጀሚሮ በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ እየተካሄደ ነው።

በዓውደጥናቱ ላይ በሚኒስቴሩ የኢነርጂ ጥናትና ክትትል ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ጎሳዬ መንግስቴ እንደገለጹት በሀገሪቱ የኢነርጂ ልማት ለማስፋፋት መንግስት በተደራሽ ኃይል ኢነርጂ ልማት ፕሮግራም ላይ በርካታ የማስፋፋት ስራ እያከናወነ ነው።

እስካሁን በተከናወኑ የታዳሽ ኃይል ኢነርጂ ስራዎች የሀገሪቱ 53 በመቶ አካባቢዎች የኤሌትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ከመሆናቸው በተጨማሪ ለጎረቤት ሀገራትም ከዘርፉ የተገኘውን ውጤት ማድረስ መቻሉን አስታውቀዋል።

የታዳሽ ኃይል ኢነርጂ ግንባታ በዓለም ላይ የተከሰተውን የካርቦን ልቀት በመከላከል ረገድ ትኩረት የተሰጠው በመሆኑ በሀገሪቱ የኢኮኖሚ እድገት ላይ ጉልህ ሚና ከማበርከት በተጨማሪ ሀገሪቱን መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለማሰለፍ የሚደረገውን ጥረት እንደሚያፋውገልጸዋል። የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት ስትራቴጂን ለማሳካት በተፋሰስ ልማትና ሌሎች እንቅስቃሴዎች ላይ ለአካባቢ ልማት ጥበቃ ትኩረት በመስጠት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። የታዳሽ ኢነርጂ ኃይልና የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂዎችን ለማጠናከር ሚኒስቴሩ ከተለያዩ ከፍተኛ ትምህርትና ምርምር ተቋማት ጋር ስራዎችን በቅንጅት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

የታዳሽ ኃይል ኢነርጂን ለማስፋፋት እየተከናወነ ያለው አበረታች እንቅስቃሴ ለማጎልበት የጥናትና ምርምር ስራው ከፍተኛ አስተዋጽ ስለሚያበረክት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተናግረዋል።

የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የተፈጥሮ ሳይንስና ስነ-ቀመር ኮሌጅ ዲን ዶክተር ጌታቸው አበበ ዩኒቨርሲቲው የሰለጠነ የሰው ኃይል በጥራትና በብቃት በማፍራት፣ የጥናትና ምርምር ስራ በማካሄድ ምርታማነትን ለማሳደግ ለሚደረገው ጥረት ድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል።

የዓውደ ጥናቱ አላማ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚካሄዱ የጥናትና ምርምር ስራዎች መንግስት የሚያካሂደውን የልማት ስራ ለማጠናከር የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል።

ነገ በሚጠናቀቀው ዓውደጥናት ላይ ከሀገሪቱ የከፍተኛ ትምህርትና ምርምር ተቋማት፣ ከውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር የተውጣጡ ምሁራንና ተወካዮች በታዳሽ ኢነርጂ ኃይል አቅርቦት፣ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማትና አካባቢ ጥበቃ ላይ 31 ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበው ውይይት እንደሚካሄድ ከወጣው መርሃ ግብር ለማወቅ ተችሏል።