በከፍተኛ ትምህርት ተቋም የሚማሩ ተማሪዎች በተቋሙ ውስጥ በሚኖራቸው የመማር ማስተማር ቆይታ የመቻቻልና የመረዳዳት ባህልን ካዳበሩ ውጤታማ መሆን እንደሚችሉ ፕሮፌሰር አለምጸሃይ መኮንን ገለጹ።

በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ ዝግጅቶች ሲከበር የቆየው የተማሪዎች ቀን በዓል ተጠናቀቀ።

በበዓሉ ማጠናቀቂያ ፕሮግራም ላይ በክብር እንግድነት የተገኙትም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሴል ባይሎጂ መምህርና ተመራማሪ ፕሮፌሰር አለምጸሃይ መኮንን ለዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ተሞክሮዎችን አካፍለዋል።

ፕሮፌሰር አለምጸሃይ መኮንን እ.አ.አ በ2009 በሂዩማን ፊዚዎሎጂ ኤንድ ሴል ባውሎጂ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ ያገኙና በሀገሪቱም ብቸኛዋ ሴት ፕሮፌሰር ናቸው።


በዕለቱም ፕሮፌሰር አለምጸሃይ መኮንን ለተማሪዎቹ ባስተላለፉት የተሞክሮ መልዕክት እንደገለጹት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሀገሪቱ ለምታከናውነው ቀጣይነት ያለው የልማት ጉዞ የተማረ የሰው ሃይል የሚፈራበት ተቋም ነው።

በተለይ በአሁኑ ወቅት መንግስት ለትምህርት በሰጠው ትኩረት በሀገሪቱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትም ሆነ ወደ ተቋሙ የሚገቡ የተማሪዎች ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ ማደጉንና የተማረ የሰው ሃይልም በበቂ ሁኔታ እየፈራ መሆኑን ገልጸዋል።

ተማሪዎችም በተቋሙ በሚኖራቸው የመማር ማስተማር ቆይታ ወቅት የሚያጥሙ ችግሮችን እርስ በእርስ በመነጋገር፣ በመወያየት፣በመረዳዳትና በመቻቻል ካሳለፉት ውጤታማ ሆነው መመረቅ እንደሚችሉ አስረድተዋል።

እንዲሁም ተማሪዎች በትምህርታቸው ላይ ጠንክረው እንዳይሰሩ ከሚዳርጉ፣ ከሚያዘናጉና ከሌሎች አልባሌ ነገሮች ተቆጥበው በትምህርታቸው ላይ ብቻ ካተኮሩ ወገንና ሀገርን መርዳት እንደሚችሉም አስረድተዋል።

የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፈሰር ጨመዳ ፊኒንሳ በበኩላቸው የበዓሉ መከበር በተማሪዎች መካከል ያለውን ሰላማዊ የመማር ማስተማር ስራ ይበልጥ ያጎለብታል።

እንዲሁም ተማሪዎች በተቋሙ ቆይታቸው ወቅት የባህል ልውውጥ እንዲያካሂዱና ተማሪዎች ያላቸውንም የተለያዩ ፈጠራና ታለንት ለሌሎች እንዲያካፍሉ እገዛ ያደርጋል ብለዋል።

የዩኒቨርሲቲው የ3ኛ ዓመት የሲቪል ምህንድስናና የሁለተኛ ዓመት የገጠር ግብርና ስርጸት ትምህርት ክፍል ተማሪ ፍሪያድ መሀሙድና ተማሪ ማህደር ግዛው በሰጡት አስተያየት የተማሪዎች ቀን በተቋሙ መከበሩ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ስራ እንዲጎለብት ያደርጋል።

እንዲሁም ተማሪዎች የተለያዩ ባህሎችንና የታለንት ክህሎቶችን በመለዋወጥ እርስ በርስ እንዲማማሩና እንዲለዋወጡ ማድረጉን ገልጸው፤ በተለይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሴል ባይሎጂ መምህርና ተመራማሪ ፕሮፌሰር አለምጸሃይ መኮንን በሰጧቸው ተሞክሮ ብዙ እውቀቶችን እንዳገኙ ተናግረዋል።

በዩኒቨርሲቲ ለአንድ ሳምንት በቆየው የተማሪዎች ቀን በዓል የባህል፣የኪነ ጥበብና የፈጠራ ስራ ውድድር በተማሪዎቹ መካከል የተደረገ ሲሆን ለአሸናፊዎቹም የተዘጋጀላቸውን የሞባይል ቀፎ ሽልማት በክብር እንግድነት ከተገኙት ከፕሮፌሰር አለምጸሃይ መኮንንና ከዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፈሰር ጨመዳ ፊኒንሳ እጅ ተቀብለዋል።