የጤና ሳይንስ ኮሌጅ የጤና ትምህርትና አገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን ለማስጠበቅ እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን ለማጠናከርና ግንዛቤ ለመፍጠር እንዲያስችል በየዓመቱ ለአንድ ሳምንት የሚቆይ “የጥራት ሳምንት ” ለማክበር በማቀድ በዚህ ዓመት የመጀመሪያውን ዝግጅት አካሂዷል ፡፡

በዚህ የጥራት ሳምንት ዝግጅት መክፈቻ ስነ ስርዓት ላይ ተማሪዎች ፣ መምህራን ፣ የህክምና ባለሞያዎች ፣ የዩኒቨርሲቲው የአስተዳደር አካላት የተገኙ ሲሆን በዕለቱም የትምህርትና የአገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን የተመለከቱ ጹሁፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል ፡፡

የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የጤናና ህክምና ሳይንስ ኮሌጅ ቺፍ ኤግዚኪዩቲፍ ዳይሬክተር የሆኑት ዶ/ር ያደታ ደሴ እንደተናገሩት በሀገር አቀፍ ደረጃ ጥራትን ለማስጠበቅ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሆነና በዚህም መሰረት ኮሌጁ የህክምና ትምህርት እና የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ጥራት የተፈለገው ደረጃ እንዲደርስ እያከናወነ ያላቸውን ስራዎች አጠናክሮ ለመቀጠል እንዲረዳ በጥራት ላይ የሚያተኩር ቀጣይነት ያለው ስራ እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል ፡፡

ዶ/ር ያደታ አያይዘውም የዝግጅቱ ዋና ዓላማ በየመስኩ ለጥራት ቅድሚያ ሰጥቶ መስራት ላይ በተለያዩ መንገዶች ውይይቶች እንዲደረጉና ግንዛቤ እንዲፈጠር በዚህም መምህሩና ተማሪው በመማር ማስተማር ሂደት ውስጥ እንዲሁም የጤና ባለሞያው አገልግሎት በሚሰጥበት ወቅት ጥራት ላይ ትኩረት አድርገው እንዲሰሩ ብሎም በጥራት መስራትን እንደ ባህል አድርገው እንዲይዙ ግንዛቤ ለመፍጠር እንደሆነ ተናግረዋል ፡፡

የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፕ/ር ጨመዳ ፊኒንሳ በመክፈቻ ፕሮግራሙ ላይ ባደረጉት ንግግር ኮሌጁ ለተማሪዎች ጥራት ያለው ትምህርት በመስጠትና እውቀት እንዲጨብጡ በማድረግ እንዲሁም በስሩ ባሉ የጤና አገልገሎት መስጫ ተቋማት ተግልጋዩን የሚያረካ ብቁ አገልግሎት ለመስጠት ጠንክሮ መስራት እንደሚገባው ተናግረዋል ፡፡

አያይዘውም ጥራትን ለማስጠበቅ እንደተቋም በአንድ መንፈስ በጋራ ተቀናጅቶ የመስራት ልምድ ሊዳብር እንደሚገባና ለዚህም በኮሌጁ የተዘጋጀው የጥራት ሳምንት ግንዛቤን ለማስጨበጥና ለአንድ አላማ በጋራ የመስራት ልምድን የሚዳብር በመሆኑ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ገልጸዋል ፡፡

የትምህርትና የጤና አገልግሎት ጥራትን በተመለከተ የጋራ ግንዛቤ መፍጠር ዓላማው ያደረገው ዝግጅት ለአንድ ሳምንት በጥራት ላይ ያተኮሩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርቶችን ለመስጠት፣ የአካባቢ ንጽህና ዘመቻ እና የተለያዩ ስፖርታዊ ውድድሮችን በማካሄድ ተከብሯል ፡፡

የተለያዩ አዝናኝና አስተማሪ ዝግጅቶችን በማካተት ለአንድ ሳምንት በተካሄደው ዝግጅት ላይ ተሳታፊ የነበሩት መምህር አብዲ ኢብራሂምና ተማሪ አብደላ ገመቹ በበኩላቸው እንደገለጹት የጥራት ሳምንት በመከበሩ በሀገር ደረጃ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የተቀመጡ አቅጣጫዎች ምን ለመረዳት ፣ እንደ ዩኒቨርሲቲም ምን እንደታቀደና እየተሰራ እንደሆነ እንዲሁም ጥራትን ለማስጠበቅ እንደ ግለሰብ ድርሻችው ምን እንደሆነ ግንዛቤ ለመጨበጥ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል፡፡