ኢዜአ/ሐረር/ ሐምሌ 5/2006
የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በተለያየ የትምህርት መስክ ያሰለጠናቸውን ከአምስት ሺህ 706 የሚበልጡ ተማሪዎችን በመጀመሪያ፣በሁለተኛና በዶክትሬት ድግሪ አስመረቀ።

የኦሮምያ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድርና የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሰበሳቢ አቶ አብዱልአዚዝ መሐመድና በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የካቢኔ ጉዳይዎች ሚንስትር አቶ እሸቱ ደሴ ለተማሪዎቹ ድግሪና በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት ላመጡ ዋንጫና ሜዳልያ ሰጥተዋል፡፡

በምረቃው ወቅት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዜዳንት ዶክተር ግርማ አመንቴ እንደተናገሩት ዩኒቨርሲቲው ካስመረቃቸው ተማሪዎች መካከል 22ቱ በዶክትሬት፣633ቱ በሁለተኛ ዲግሪና ቀሪዎቹ በመጀመሪያ ዲግሪ የተመረቁ ናቸው።

ተመራቂዎቹ በመደበኛ፣ በተከታታይ፣በርቀትና በክረምት መርሃ ግብር በግብርና፣በአካባቢ ሳይንስ፣ በአግሮ ኢንዱስትሪና መሬት ሃብት፣ በቢዝነስና ኢኮኖሚክስ፣በትምህርት፣በጤና ህክምና በማህበረሰብ ሳይንስና ሌሎች የትምህርት ዘርፎች ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

ዩኒቨርሲቲው በ2006 ትምህርት ዘመን በመደበኛና ተከታታይ መርሃ ግብር፣በቅድመና ድህረ ምረቃ ፕሮግራም አጠቃላይ የተማሪ ቅበላ አቅሙ ከ34 ሺህ በላይ ማድረሱን ፕሬዝዳንቱ ጠቁመው ከእነዚህም መካከል ከአምስት ሺህ በላይ የድህረ ምረቃ ተማሪዎች መሆናቸውን ገልጸዋል።

ተመራቂ ተማሪዎቹ ሀገሪቱ የነደፈቻቸውን እቅዶች፣የልማት ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎችን ለማስፈጸም ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡

እጩ ተመራቂዎቹ የቀሰሙትን እውቀት፣ ክህሎትና ዝንባሌ በሚሰማሩበት የስራ መስኮች ሀገራቸውንና ህዝባቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ የአደራ መልክት አስተላልፈዋል።

የኦሮምያ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድርና የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሰበሳቢ አቶ አብዱልአዚዝ መሐመድ ለተመራቂዎቹ ዲግሪና በትምህርታቸው ብልጫ ዋንጫና ሜዳልያ ከሰጡ በኋላ እንደተናገሩት ተመራቂዎቹ የህብረተሰቡን ችግር የሚፈቱ ጥናትና ምርምር በማካሄድ የተማሩትን ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል።

ወጣት ምሁራን ስራ ፈጣሪና ታታሪ በመሆን ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ማገዝ እንደሚገባቸው ጠቁመው ህብረተሰቡን በቅንነትና በታማኝነት በማገልገል ለሌሎች ወጣቶች አርዓያ መሆን እንደሚገባቸውም ገልጸዋል።

ከተመራቂዎች መካከል የእጽዋት ሳይንስ፣የህግ፣ የአግሮ ሳይንስና የእንግሊዘኛ ቋንቋ ተመራቂ ተማሪ ቱሉ ታደሰ፣ነስረዲን አብዱራህማን፣ጀማል አብዲና ሐዊ ንጉሴ በሰለጠኑበት ሙያ ሀገራቸውንና ያስተማራቸውን ህዝብ ለማገልገል ጠንክረው ይሰራሉ።