ድሬዳዋ መጋቢት 2/2009 በሀገሪቱ የተጀመሩ ለውጦችን ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግሩ ችግር ፈቺ የምርምር ሥራዎችን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሀረማያ ዩኒቨርሲቲ
መምህራንና ሠራተኞች አስታወቁ፡፡

በዋና ግቢና በሐረር ካምፓስ የሚገኙ ከ4 ሺህ በላይ የዩኒቨርስቲው መምህራንና የአስተዳደር ሠራተኞች ላለፉት አምስት ቀናት ሲያካሄዱ የቆዩትን የተሀድሶ ግምገማ
ትናንት አጠናቀዋል፡፡
መምህራኑና ሠራተኞቹ ባወጡት የአቋም መግለጫ እንዳመለከቱት በሀገሪቱ የተመዘገቡ ውጤቶችና ተግዳሮቶች ላይ በጥልቀት ተወያይተዋል፡፡

በዩኒቨርሲቲው የተልዕኮ ስኬቶች፣ በሚስተዋሉ ችግሮችና መፍትሄዎች ላይ የጋራና የተናጥል ግምገማ አድርገዋል፡፡
የተለዩ ሰፋፊ ጉድለቶችን በማያዳግም መንገድ ለመፍታት በቁርጠኝነት እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል፡፡
የዩኒቨርሲቲውን ተልዕኮ የሚያደናቅፋ የመልካም አስተዳደርና የኪራይ ሰብሳቢነት ችግሮችን ለመፍታት ተግተው እንደሚሰሩም በአቋም መግለጫቸው ላይ አመለክተዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በሀገሪቱ ለተመዘገቡት ማህበራዊ፣ ምጣኔ ሃብታዊ ፣ፖለቲካዊ ለውጦችና እድገቶች አስተዋጽኦ ያበረከተ የተማረ የሰው ሃይል በማፍራት የድርሻውን ሲወጣ
ቆይቷል፡፡
ችግር ፈቺ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርምር ውጤቶችን ለተጠቃሚ ከማስተላለፍ ባሻገር የማህበረሰብ ችግርን የሚፈቱ ሥራዎች መተግበራቸውንም ጠቁመዋል፡፡
እነዚህን ውጤቶች በላቀ ደረጃ ለማሸጋገርና በሀገረቱ እየተመዘገቡ የሚገኙ እድገቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል ከአመራር እስከ ድጋፍ ሰጪው ሠራተኛ የድርሻውን ለመወጣት
የተሃድሶው ግምገማው መነቃቃት መፍጠሩንም ጠቅሰዋል፡፡
ብልሹ አሠራሮችንና አመለካከቶችን ሥር ነቀል በሆነ መንገድ በማስወገድ ሠላማዊ የመማር ማስተማር ተግባሩን ቀጣይነት ለማረጋገጥ እንደሚተጉም ተመልክቷል፡፡

” ብቁና ውጤታማ የትምህርት ማህበረሰብ ለትምህርት ጥራትና ለሀገር ህዳሴ” በሚል መሪ ሃሳብ በተካሄደው የጥልቅ ተሃድሶ መድረክ በተፈጠረው መነቃቃት በመታገዝ በቀጣይ
የዩኒቨርሲቲውን ተልዕኮ በላቀ ደረጃ ለመፈፀም እንደሚተጉ አስተያየታቸው ለኢዜአ የሰጡ  ሠራተኞችና መምህራን ተናግረዋል፡፡
የዩኒቨርሲቲው የተቋማዊ ልማትና ፋሲሊቲ አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ሙክታር ዳዊት “መድረኩ ጥራት ያለው ትምህርት እንዲሰፍን ፣ሰላማዊ የመማር
ማስተማር ተግባሩ ዘላቂነት እንዲረጋገጥ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሮበታል “ብለዋል፡፡
የሚመሩት ክፍል ከግብአትና ከአቅርቦት እንዲሁም ከሌሎች አገልገሎቶች አኳያ ትልቅ ሃላፊነት እንዳለበት አመልክተው ክፍሉ ያሉበትን ችግሮች በፍጥነት በመፍታት ለውጥ
ለማምጣት በትጋት አንደሚሰሩም ተናግረዋል፡፡
የጂኦግራፊና የአካባቢ ጥናት ትምህርት ክፍል መምህር ብንያም ጌታቸው “መድረኩ በመምህርነቴ የተማረና ብቁ ዜጋ ለማፍራት፣ተልዕኮዬን በተሻለ ደረጃ ለመወጣት፣
የምርምርና የጥናት ሥራዎችን ይበልጥ እንድሰራ መነቃቃት ፈጥሮልኛል” ብለዋል፡፡

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ጨመዳ ፊኒንሳ በበኩላቸው የተሃድሶው መድረክ መምህራንና ሠራተኛው የልማታዊ መንግስትን ፖሊሲዎችና አቅጣጫዎች በተሻለ መንገድ
ማስገንዘብ እንዳስቻለ ገልጸዋል፡፡ ተቋሙም ይህንኑ ተልዕኮ በተሻለ መንገድ ለመፈፀም እንደሚያግዘውም ተናግረዋል፡፡
የዩኒቨርሲቲው የቦርድ አባል አቶ ሴኮቱሬ ጌታቸው እንዳሉትም የተሀድሶ ግምገማውን ማካሄድ ያስፈለገው ችግሮችን በማረም ለሀገራዊና ተቋማዊ ለውጥ የሚተጉ ውጤታማ
ምሁራንን እንዲሁም ለህዝብ የመልካም አስተዳደር ችግሮች መፍትሄ ለማምጣት የሚተጉ ሰራተኞችን ለመፍጠር ነው፡፡