የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ማዕከላዊ ፋይናንስ የሠራተኞቹን አቅም በማጎልበት ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እንዲያስችለው ከ50 ለሚበልጡ የሂሳብ ባለሙያዎቹ ለሰባት ተከታታይ ቀናት ስልጠና ሰጠ፡፡

ስልጠናው የመንግስት ሂሳብ አያያዝ እንቅስቃሴን ለማዘመን እንዲቻል የአይቤክስ የፋይናንሽያል ማኔጅሜንት ሶፍትዌርን በመጠቀምና የሰለጠኑ የዘርፉ ባለሙያዎችን በማፍራት በጀትን በሚገባ ለማስተዳደር ፣ የተቋሙን ፋይናንስ የሚያሳዩ መዛግብቶችን በጥራት ለመያዝና መረጃቸውን ወደ ኤሌክትሮኒክስ የመረጃ ›ÁÁ´ ዘዴ በሚገባ ለመጠቀም እንዲችሉ የሚያስችል ነው፡፡
የአንድ ተቋም ሀብት በሚገባ ተይዞ ኢኮኖሚያዊ ብቃት ባለው አሰራር ለታለመለት ዓላማ ብቻ ሥራ ላይ እንዲውል የፋይናንስ መረጃው በዘመናዊ ቴክኖሎጂ መታገዝ እንዳለበት የዩኒቨርሲቲው ማዕከላዊ ፋይናንስ አስተባባሪ የሆኑት አቶ ይነበብ አለሙ ተናግረዋል፡፡

አቶ ይነበብ አያይዘው እንደገለጹት ስልጠናው በተቋሙ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደተሰጠ ጠቅሰው የሂሳብ ባለሙያዎችን አቅም ከማጎለበት በተጨማሪ የመንግስት ገንዘብ ለተቀመጠለት ዓላማ ብቻ እንዲውል ለማድረግ የሚያግዝ ነው ብለዋል፡፡
የስልጠናው ተካፋዮችም ስልጠናው የፋይናንስ አሰራርን ግልጽ በሆነና ስታንዳርዱን በጠበቀ መልኩ በማካሄድ የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠት እንዲችሉ የሚረዳ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

ስልጠናው የተሰጠው ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ትብብር ሚኒስተር በመጡ ባለሙያተኞች ሲሆን በሁለት ዙር ሁሉም የፋይናንስ ባለሙያዎች እንዲሰለጥኑ ተደርጓል ፡፡