በፍጹም ፍሰሀ
ኮሌጁ የሚሰጠውን ትምህርት ጥራት ለማስጠበቅ የሚያስችሉ ግብዓቶችን እያሟላ መሆኑ ተገለጸ፡፡
የህግ ኮሌጁን የሚቀላቀሉ አዲስ ተማሪዎችን ለመቀበልና ከነባር ተማሪዎችና መምህራን ጋር ለማስተዋወቅና የልምድ ልውውጥ የሚካሄድበት ዓመታዊ መድረክ ከህግ ተማሪዎች ማህበር ጋር በመተባበር ሰሞኑን ተካሂዶ ነበር፡፡
በመድረኩ ላይ የኮሌጁ አዲስና ነባር ተማሪዎች እንዲሁም መምህራንና ሰራተኞች የተገኙ ሲሆን በዕለቱም አጠቅላይ የአካዳሚክ ኦረንቴሽንና የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ዶ/ር ሪቻርድ ዌንዝል ተደርጓል፡፡
ዶ/ር ሪቻርድ ዌንዝል በንግግራቸው ተማሪዎቻችን በሀገርና ዓለም ዓቀፍ ደረጃ በምስለ ችሎት ውድድር ጥሩ ውጤት እያስመዘገቡ እንደሆነና ኮሌጁ ጥራት ያለው ትምህርት ለመስጠት የሚያስፈልጉ ግብዓቶችንና መምህራንን እያሟላ በመሆኑ አዲስ ገቢ ተማሪዎችንም ብቁ ዜጋ እንዲሆኑ ጥራት ያለው ትምህርት ለመስጠት ኮሌጁ ዝግጁ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

ኮሌጁ ለሚሰጠው ትምህርት አጋዥ የሚሆኑ መጽሀፍትን በቅርቡ በእርዳታ በማስገባቱ እንዲሁም የመምህራኖቹን የትምህርት ዝግጁነት በየጊዜው እንዲሻሻል በመደረጉት ጥራት ያለው ትምህርት ለመስጠት እንደሚያግዝ ዶ/ር ሪቻርድ ጠቁመው በኮሌጁ ውስጥ ያሉ መምህራንና ተማሪዎች ግንኙነት ቤተሰባዊ በመሆኑ ተማሪዎቻችን ውጤታማ እንዲሆኑ አስተዋጽዖ አበርክቷል ብለዋል፡፡
የህግ ተማሪዎች ማህበር ተወካይ ተማሪ ሙሉቀን ሰኢድን የማህበሩን ዓላማና ተግባር በተመለከተም ለአዲስ ተማሪዎቹ ማብራሪያ ሰጥቷል ፡፡ አዲስ ገቢ ተማሪዎች መልካም ተሞክሮን ይቀስሙ ዘንድም አርዓያ የሚሆኑ መምህራንና ነባር ተማሪዎች በዝግጅቱ ላይ ተገኝተው ልምዳቸውን አካፍለዋል ፡፡

በዝግጁቱ ላይ የተካፈሉ አዲስ ገቢ ተማሪዎች እንደገለጹት መድረኩ አስተማሪና በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው ስኬታማ በመሆን ጥሩ ጊዜ ማሳለፍ ይችሉ ዘንድ ትልቅ ልምድ ያገኙበት እንደነበር ገልጸው ለተደረገላቸው አቀባበልም ለህግ ኮሌጁና ለህግ ተማሪዎች ማህበር ምስጋናቸውን አቅርበዋል ፡፡