የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ባሳለፍነው ሳምንት የኮሮና ቫይረሥ ስርጭትን የመከላከል ስራ ላይ ለማሰማራት ያሰለጠናቸውን በጎፈቃደኞች ዛሬ ሥራ እንዲጀምሩ አደረገ።

በጎ ፈቃደኞቹ ሥራ ሲጀምሩ መልዕክት ያስተላለፉት

የአስተዳደርና ተማሪዎች ጉዳይ ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ጄይላን ወልዪ ኮሮና ድሃና ሀብታም ሳይለይ ዓለምን በአንድነት እያስጨነቀ ያለው ተላላፊ በሽታ እጅግ አደገኛ በመሆኑ በመከላከሉ ስራ ላይ ሁሉም ራሱን ከመጠበቅ ጀምሮ ሊሳተፍና ኃላፊነቱን ሊወጣ ካልቻለ በማህበረሰባችን ላይ የሚደርሰው ጉዳት ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል የሌሎች ሃገሮችን ተሞክሮ በማየት መገመት ይቻላል ብለዋል፡፡

ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ያደረገውን የዜግነት አገልግሎት ጥሪ ተቀብለው ማህበረሰቡን ለማስተማር የተሰባሠቡ በጎ ፈቃደኞችን ፕሮፌሰር ጄይላን በራሴና በዩኒቨርሲቲው ስም አመሰግናለሁ ብለዋል፡፡

ባቴ ላይ በተካሄደው መክፈቻ ስነስርዓት ላይ የተገኙት የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር መንግሥቱ ኡርጌ በበኩላቸው የምስራቅ ኢትዮጵያ በርካታ የሰዎች እንቅስቃሴ ያለበት መተላለፊያ በመሆኑ ለቫይረሱ የመጋለጥ ዕድላችን ከፍተኛ ሥለሆነ በተለያዩ መንገዶች የሚተላለፉ የጥንቃቄ መልዕክቶች ተግባራዊ ልናደርግና መልዕክቱንም ለማህበረሰባችን ልናስተላልፍ ይገባናል ብለዋል።

የኮሮና ቫይረስ ሥርጭትን ለመከላከል በሐረማያ ዙሪያ ቤት ለቤት እየሄዱ ለማስተማር ከ172 በላይ ተማሪዎችና ከ50 በላይ መምህራን በበጎ ፈቃደኛነት የቤት ለቤት ትምህርት ለመስጠት በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ዙሪያ ዛሬ ተሰማርተል፡፡ መምህራኑ ከዋናው ግቢ እስከ ሐረማያ ከተማ የእግር ጉዞ በማድረግ አስተምረዋል።

በጎ ፈቃደኞቹ በሐረማያና አወዳይ ከተሞች የኮሮና ቫይረስ የመከላከያ መንገዶችን በተመለከተ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ የሰሩ ሲሆን የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶክተር ጀማል ዩሱፍ በግንዛቤ ማስጨበጥ ስራው ላይ ተሳትፈዋል።

ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ሥልጠና የሰጣቸው በቁሉቢና ጨለንቆ ከተሞች የሚገኙ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ቤት ለቤት እየሄዱ የኮሮና ቫይረስ መከላከያ መንገዶችን የተመለከተ ትምህርት መስጠታቸውን ከአስተባባሪዎቹ ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል።

ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ

ሚያዚያ 5 ቀን 2012 ዓ.ም