በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዚዳንት ጽ/ቤት በዩኒቨርሲቲው በሚዛናዊ የውጤት ተኮርና የትምህርት ልማት ሰራዊት ግንባታ ዙሪያ በተለያየ ደረጃ ለሚገኙ አመራር አካላት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ፡፡

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ፕሮፌሰር ጨመዳ ፊኒንሳ በመክፈቻ ንግግራቸው እንደገለጹት በአገሪቷ ከሚገኙ ቀደምት ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ የሆነው የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ጥራትን በማስጠበቅ ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋ በማፍራትና እየተካሄዱ የሚገኙትን የኢኮኖሚ፣ማህበራዊና ሌሎች ልማቶችን በመደገፍ ሞዴል በመሆን አገሪቱ ለተያያዘችው የልማት ስራዎች መፋጠን በሚደረገው ጥረት የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ገልፀዋል፡፡በቀጣይም የመማር ማስተማር፣ የተማሪዎች ምዘና፣ የምርምርና የማህበረሰብ አገልግሎት የጥራት ደረጃን በማስጠበቅ፣ እንዲሁም ውጤታማ የትምህርት እንቅስቃሴ እንዲኖር ተገቢውን ክትትልና ድጋፍ  እንደሚደረግ ተናግረዋል፡፡

ፕሮፌሰር ጨመዳ በማያያዝም የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥና ሁለንተናዊ ለውጥ ለማምጣት ዩኒቨርሲቲው ዕቅዱን በተደራጀ የትምህርትና ቴክኖሎጂ ልማት ሰራዊት አቅም የመተግበር ሥራዎችን መጀመሩን ጠቁመው ሥልጠናው በአፈጻጸም ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን ለመሙላት እንደሚያስችል ጠቁመው በቀጣይም ለዩኒቨርሲቲው ሥራ ስኬት በትምህርትና ቴክኖሎጂ ልማት ሰራዊት ግንባታ ዙሪያ ተደጋጋሚ ስልጠናዎችን በመስጠት የጠራ ግንዛቤ እንዲፈጠር  ይደረጋል ብለዋል፡፡

የአካዳሚክ ፕሮግራሞች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶክተር ይልፋሸዋ ስዩም እንደተናገሩት ዳይሬክቶሬቱ በ2008 የበጀት ዓመት ለመስራት ያቀዳቸውን ተግባራት ከሁሉም የስራ ክፍሎች ጋር ውጤታማ፣ ጠንካራና ጤናማ የሆነ የስራ ግንኙነት በመፍጠር ጥራቱ የተረጋገጠ የመማር ማስተማር ሂደት፣ጥናትና ምርምር እንዲሁም የማህበረሰብ አገልግሎትን እዉን ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ገልፃዋል፡፡

ስልጠናው በማስፈፀሚያ ስልቶች፣በውጤት ተኮር ሥርዓት ምዘና (BSC) በእቅድ አወጣጥና አፈፃፀም፣ሪፖርት አቀራረብና መረጃ አሰባሰብ ላይ ያተኮረና ከትምህርት ሚኒስቴር በመጡ ባለሙያዎችና በዩኒቨርሲቲው የዕቅድና ተቋማዊ ለውጥ ዳይሬክቶሬት ከፍተኛ ባለሙያዎች ተሰጥቷል፡፡

በስልጠናዉ ከየኮሌጆች የተወጣጡ ከ70 በላይ አመራሮችና ጉዳዩ የሚመለከታቸዉ የዩኒቨርሲቲው አካላት የተሳተፉ ሲሆን በቀጣይ በየደረጃው ላሉ ሰራተኞችና ተማሪዎች ተከታታይ ስልጠናዎች እንደሚሰጡና አስፈላጊው ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡

በስልጠናዉ ማጠቃለያ ለይ ፕሮፌሰር ንጉሴ ደቻሳ የአካዳሚክ ጉዳዮችም/ፕሬዚዳንት  ባደረጉት ንግግር፣የዚህ አይነት ስልጠና የአመራሩን አቅም በማጎልበት ረገድ ያለዉ ሚና ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዉ ሰልጣኞች በስልጠና ያገኙትን እዉቀት ለሌሎች በማስተለላፍ፣በተግባር በመተርጎምና ዉጤት ማስመዝገብ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡