በሀረማያ ዩኒቨርሲቲና በአንድ ግብረሰናይ አለም አቀፍ ድርጅት በምርምር የተለዩ ምርጥ የቲማቲም ዘሮች ለአርሶአደሩ ለማቅረብ ዝግጅት መጠናቀቁን የሀረማያ ዩኒቨርሲቲ ገለፀ፡፡የሚሰጣቸው ዘር ምርታማነታቸውን በማሳደግ ገቢያቸውን እንደሚጨምር የድሬዳዋ አርሶአደሮች ተናግረዋል፡፡

ፌርፕላኔት የእስራኤል አለምአቀፍ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ከሀረማያ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመሆን በድሬዳዋ የግብርና ምርምር መከወኛ በሆነው ቶኒፋርማ 31 ምርጥ የቲማቲም ዝርያዎችን በመትከል የተሻለ ምርት የሚሰጡና በሽታ መቋቋም የሚችሉትን መለየት ችሏል፡፡

ይህንኑ ውጤት ለመገምገም በተካሄደ የመስክ ጉብኝት ላይ የተገኙት አርሶአደሮች በተግባር የተረጋገጡት ምርጥ ዘሮች ተሰራጭተውላቸው ለመጠቀም እንዳነሳቸው አስታውቀዋል፡፡

ከቲማቲም አብቃይ መካክል አርሶአደር መሐመድ ረሺድ ኡስማን ሁሴን በየዓመቱ የሚዘሩት ቲማንቲም ምርት የሚያጓጓ ቢሆንም ድንገት በሚከሰት በሽታ ልፋታቸውን ባዶ እንደሚያደርገው ገልፀዋል፡፡ የአሁኑ ምርጥ ዘር ይህን ችግር የሚቋቋምና ይበልጥ ምርትን የሚያሳድግ በመሆኑ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ያፋጥነዋል ብለዋል፡፡

የሀረማያ ዩኒቨርሲቲ በምርምር የተረጋገጡ የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም የሰብል ዝርያዎችን ለአርሶአደሩ በማሰራጨት የገጠሩን ህብረተሰብ ህይወት ትርጉም ባለው መንገድ እንዲለወጥ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን የዩኒቨርሲቲና የማህበረሰብ ተሳትፎና ኢንተርፕራይዝ ልማት ምክትልና ፕሬዘዳንት ፕሮፌሰር ከበደ ወ/ጻድቅ አስታውቀዋል፡፡

ይህንኑ ተግባር መሰረት በማድረግ ከፌርፕላኔት ጋር ለሀረማያና ለድሬዳዋ ቲማንቲም አብቃይ አርሶአደሮች የየአካባቢያቸውን ሥነ-ምህዳርና አየር ንብረት የሚቋቋሙና ውጤታማነታቸው በመስክ እየተገመገመ የሚገኙ ምርጥ ዘሮችን ለማሰራጨት እየተሰራ መሆኑን ፕሮፌሰር ከበደ ገልፀዋል፡፡

የፌርፕላኔት መስራችና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ሾሻን ሐራን በበኩላቸው በታዳጊ ሀገሮች ለሚገኙ አነስተኛ ገቢያቸው አርሶአደሮች በቀላሉ ከየአካባቢ አግሮ-ኢኮሎጂ ጋር የሚስማሙና በየአካባቢው በቀላሉ ምርታማ የአትክልት ዝርያዎችን እንደሚያሰራጭ ገልፀዋል፡፡ዝርያዎቹ ምርትን በአምስት እጥፍ የሚያሳድግና በሽታን በፅናት መቋቋም የሚችሉ መሆናቸውን ዶ/ር ሾሻን ተናግረው ስለዘሮቹ ተገቢውን ሥልጠና ለባለሙያዎችና ለአርሶአደሮች በመስጠት ጥቅም ላይ እንዲውል ይደረጋል ብለዋል፡፡

ከወር በኃላ ከአስተዳደሩ ግብርና ቢሮና ከገበሬዎች ዩኒየን ጋር በመሆን ዘር የማሰራጨቱ ሥራ እንደሚጀመር ገልፀዋል፡፡

የድሬ ሁለገብ የገበሬዎች ዩኒዬን ሥራ አስኪያጅ አቶ መድህን መኮንን በሰርቶማሳያና በምርምር የተለዩ ምርጥ የቲማቲም ዘሮች የአርሶአደሩን ምርት የሚያሳድጉና ከላቡ ተጠቃሚ እንዲሆን የሚያግዙ መሆናቸውን ተናገህረው አምራቾች የማሰራጨት ሥራ በተቀናጀ መንገድ የሚተገበር መሆኑን ጠቁመዋል፡፡